Saturday, May 6, 2017

“እርሱ በተዋሕዶ ሰው የሆነ አምላክ ነው”

“እርሱ በተዋሕዶ ሰው የሆነ አምላክ ነው”፡፡ በሚል ርእስ በክፍል አንድ እና ሁለት ተዋሕዶን ሊቁ የተዋሕዶ አርበኛ ቅዱስ ጎርጎርዮስ እንዴት እንደገለጸው አይተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ ሊቁ ቅዱስ ቄርሎስ ተዋሕዶን ለማስረዳት የመሰለውን ምሳሌ እናያለን፡፡ ከዚያ በፊት ግን ይህንን ጽሁፍ የምታነቡ ሰዎች እንድትረዱኝ የምፈልገው ነገር እኔ አባቶች በመጽሐፋቸው ላይ ያሰፈሩትን ነገር ሳልጨምር ሳልቀንስ እንደምጽፈው ልገልጽላችሁ እፈልጋለሁ፡፡ የቅባት ተከታዮች ግን እነሱ የማያውቁት ነገር ከሆነ ወይም እነሱ የሚሉትን የኑፋቄ ትምህርት የሚደግፍ መስሎ ካልታያቸው ምዕራፍ እና ቁጥር ጠቅሼ የጻፍኩትን ጽሁፍ የእራስህ ፍልስፍና ነው በማለት እነሱ እንደማይቀበሉት በክፍል አንድ እና ሁለት በሰጡት አስተያየት ላይ ለማየት ሞክሬያለሁ፡፡ ይህ ግን ፈጽሞ ከእውነት የራቀ ነው፡፡ ስለዚህ የእነሱን ማንነት ለመረዳት የሚጠቀሰውን ጥቅስ መጽሐፉ ላይ በመሔድ ማንበብ እና እውነት ወይም ሐሰት መሆኑን መረዳት ትችላላችሁ፡፡ወደ ምሳሌው ከመሔዴ በፊት የቅባት እምነት ተከታዮች ምስጢረ ስላሴ ላይ ያልገባቸው ነገር እንዳለ ትንሳኤ የሚባል ተከታያቸው ከጻፈው ጽሁፍ መረዳት ችያለሁ፡፡ ሌሎች የጻፋቸውን ነገሮች በሚቀጥሉት ከፍሎች እናያለን፡፡ መልካም ንባብ ካነበባችሁ በኋላ ሼር ማደረግን እንዳትረሱ ምክንያቱም ለሌሎች የድህነት ምክንያት ይሆናል እና ነው፡፡
ስላሴ ሶስት ከሚሆኑባቸው ነገሮች አንዱ የከዊን ሶስትነት ነው፡፡ ይህም ከዊነ ልብ፣ ከዊነ ቃል እና ከዊነ እስትንፋስ ናቸው፡፡ ምንም እንኳ ስላሴ በከዊን ሶሰት ቢሆኑም በህልውና በመገናዘብ ደግሞ እንድ ይሆናሉ፡፡ ይህም እንዴት ነው ብትሉ እንደሚከተለው ነው፡፡ ይህም ማለት በአብ ልብነት ወልድም መንፍስ ቅዱስም ያስቡበታል፡፡ በወልድ ቃልነት አብም መንፈስ ቅዱስም ይናገሩበታል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስነት(ሕይወትነት) አብም ወልድም ለዘለዓለም ሕያዋን ሆነው ይኖሩበታል፡፡ ይህ በስላሴ በህልውና የመገናዘብ ሁኔታ ቀድሞም አልተለያየም፡፡ አሁንም አልተለያየም፡፡ ወደፊትም ቢሆን አይለያይም፡፡ ይህና ያመጣሁበት ዋናው ምክንያት ሰው ምስጢረ ተዋሕዶን ለመረዳት መጀመሪያ ይህንን ረቂቅ ምስጢር መረዳት ስለሚገባ ነው፡፡ ትንሽ ስለረዘመ ነው ምሳሌው በክፍል አራት ይቀጥላል፡፡

No comments:

Post a Comment